መረጃ እና አጠቃቀሙ
መረጃን ለማግኘት ትኩረት እና ጥረት የሚጠይቅ ስራ ነው።መረጃውን የምናገኝበት ፍጥነትም
ወሳኝነት አለው።በተጨማሪም በመረጃው ውስጥ የተካተቱት ዝርዝር ሃሳቦችም ትኩረት ያሻሉ።እኛ
መረጃውን ካገኘንስ በኋላ ለማን ? እንዴት ? መቼ ? የት ቦታ ? በምን መልኩ? መረጃውን እናስተላልፈው
የሚሉት ሃሳቦች አዕምሮአችንን ውስጥ ሊመላለሱ ይችላሉ።ራሳችን ተጠቅመን ወገኖቻችንን
መጥቀም ደግሞ ስኬታማ የመረጃ አጠቃቀምን ያሳያል።
መረጃዎች ከመንግስታዊ አና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ይወጣሉ።የፖሊሲ ለውጦች እና
ማሻሻያዎች ፤ ህጎች እና አዳዲስ የመተዳደሪያ ደንቦች ፤ የገንዘብ ድጋፎች እና ድጎማዎች እንዲሁም
ዜናዎች ጊዜያቸውን ጠብቀው ይመጣሉ።መረጃዎች ቢበዙም በየመልኩ ከፋፍሎ መጠቀም ከእኛ
የሚጠበቅ ስራ ነው።
እኛ በእለት እለት ኑሮአችን ተጠምደን ስንውል እጅግ ጠቃሚ የሆኑ መረጃዎች ያመልጡናል።እነኚህን
መረጃዎች የምንፈልግበት ፡ ተጠቅመን ሌሎችን የምንጠቅምበት ጊዜ በአግባቡ አንመድብለትም።ቀኑ
ሳናውቀው ያልቅብናል።በቀኑ መጨረሻም ከድካማችን እፎይ ስንል የሚቀናን በማህበራዊ ሚዲያ ላይ
ተቀምጠን በማይጠቅሙን መረጃዎች ሰዓታችንን ማባከን ነው።ምናልባትም የሚጠቅመን መረጃ
በማህበራዊ ገጻችን እልፍ ቢል ተገቢውን ትኩረት ላንሰጠው እንችላለን።
በውጭው አለም በምንኖርበት ሃገር የመግባቢያው ቋንቋ የአፍ መፍቻ ቋንቋችን ካልሆነ
ለመረጃ ማግኘት እና መጠቀም ተጨማሪ እንቅፋት ይፈጥርብናል።በዚህ ሁኔታ መረጃውን ተረድቶ
የሚተርጉም አካል ማግኘት ትልቅ እፎይታ ይሰጣል።በተለይ መረጃዎች ከየአቅጣጫቸው ከምንጫቸው
ተሰብስበው እና ተተርጉመው በማዕከላዊ የመረጃ መድረክ መቅረብ ቢችሉ ለተጠቃሚየዎች
የተቀላጠፈ ፍሬያማ አገልግሎት እንዲያገኙ ይረዳል።
የአኩኩሉ ፋሚሊ በማህበረሰባችን የሚታየውን የመረጃ እጥረት እና የአጠቃቀም ጉድለት በመረዳት
ለወገኖቻችን ይጠቅማል የምንለውን የመረጃ እና የመገናኛ መድረክ ይዘን ቀርበናል።የአኩኩሉ ፋሚሊ
መድረክ ለእናንተ ይበጃሉ በሚላቸው በጤና ፤ በትምህርት ፤ በንግድ እና ገንዘብ አያያዝ እንዲሁም
በስፖርት እና መዝናኛ ልዩ ልዩ መረጃዎች ይዞላችሁ ይቀርባል።መረጃዎችን ከእኛ በመውሰድ እና
ለእኛም በማቀበል መረጃ የማዳረስ ድርሻዎትን ይወጡ።
በመንገናኛ ብዙሃናችን ፡ በፓድካስት ፡ በድህረ ገጻችን ፡ በስልክ ፡ በኢሜል እና በደብዳቤ
መልዕክቶቻችሁን ልትልኩልን ትችላላችሁ።
አብረን እንደግ!!!
ዶ/ር እልልታ ረጋሳ
አኩኩሉ ፋሚሊ



